የስፔን እግር ኳስ ፌዴሬሽን ከሀገር ውጭ አዲስ የውድድር ቅርፅ ሊያዘጋጅ መሆኑን እወቁልኝ ብሏል፡፡
አዲስ ይዘጋጃል የተባለው የውድድር አይነት በእንግሊዝ ኮሚዩኒቲ ሽልድ የምንለውን አይነት ሲሆን ሱፐር ኮፓ ዴ እስፓና የሚል ስያሜ እንደሚሰጠው ተነግሯል፡፡
የስፔን ፌዴሬሽን ላ ሊጋን በሌላው ዓለም ለማስተዋወቅ እና ገበያ ለማግኘት ሲሉ ወደ አሜሪካ ለመውሰድ ቢጥሩም አልተሳካም ፤ አሁን ደግሞ በአዲስ ቅርፅ ብቅ ብሏል፡፡
የስፔን የአሸናፊዎች አሸናፊ (ሱፐር ኮፓ) ስፔን ውስጥ በደርሶ መልስ ሁለት ግጥሚያዎች የሚደረጉ ሲሆን የ2018ቱ በባርሴሎና እና ሲቪያ መካከል ሞሮኮ ላይ ተካሂዶ ነበር፡፡
ሱፐር ኮፓ ዴ እስፓና በአራት ቡድኖች መካከል እንዲካሄድ የታሰበ ሲሆን የኮፓ ዴል ሬይ የፍፃሜ ተፋላሚ ቡድኖች እና የላ ሊጋ ሁለት ቀዳሚ ክለቦች ይካፈላሉ፡፡
የሮያል ስፔን አግርኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት ሊዩስ ሩቢያሌስ የሱፐር ኮፓ ዴ እስፓና የመጀመሪያው ውድድር በ2019 የስፔን ላ ሊጋ ከመጀመሩ አስቀድሞ እንዲደረግ ፍላጎት ቢኖራቸውም እስካሁን አልፀደቀም፡፡
ፕሬዚዳንቱ አዲሱ የውድድር ቅርፅ፤ በስፔን አግር ኳስ ላይ ተጨማሪ ፍላጎት እንዲመጣ ያደርጋል ብለዋል፡፡
ቢቢሲ