loading
ሚኒስቴሩ በሃብት ማሰባሰብ ስትራቴጂ ካሰባሰበዉ ሀብት ዉስጥ 15 ሚሊዮን ብሩን ድጋፍ ለሚያስፈልጋቸዉ ተቋማት አስረከበ፡፡

አዲስ አበባ፣ ሚያዚያ 22፣ 2012 ሚኒስቴሩ በሃብት ማሰባሰብ ስትራቴጂ ካሰባሰበዉ ሀብት ዉስጥ 15 ሚሊዮን ብሩን ድጋፍ ለሚያስፈልጋቸዉ ተቋማት አስረከበ፡፡የሴቶች፣ ህፃናትና ወጣቶች ሚኒስቴር ለአርትስ በላከዉ መግለጫ እንዳስታወቀዉ፤ ሚኒስቴሩ ባካሄደዉ የርክክብ ስነስርዓት ላይ የተገኙት የወጣቶች ዘርፍ ሚኒስትር ዲኤታ ወ/ሮ ህይወት ኃይሉ ባስተላለፉት መልዕክት ቫይረሱ በፍጥነት የሚዛመት በመሆኑ የቆየንበት  የመጠጋጋት፣ የመጨባበጥና የመሳሳም ልማድን መተዉ አለብን ብለዋል፡፡

ሚኒስትር ዲኤታዋ በተጨማሪም የቫይረሱን ስርጭት ለመግታት እንዲያግዝ ቀደም ሲል ከገቢዎች ሚኒስቴርና ከዓለም አቀፉ የህጻናት መርጃ ድርጅት (ዩኒሴፍ) እና ሌሎች ተቋማት  ካገኘው  16  ሚሊዮን ብር ውስጥ 15 ሚሊየን ብር የሚገመተውን የምግብ  የአልባሳትና ቁሳቁስ ድጋፍ ለተቋማት ማስረከብ በመቻሉ ደስታ እንደተሰማቸው ገልጸዋል፡፡ድጋፉን ከተረከቡት መካከል አንዷ የክበበ ህጻናት ማሳደጊያ ተቋም ኃላፊ ወ/ሮ ጥሩወርቅ ደበበ በዚህ አሰቸጋሪ ጊዜ የተደረገዉ ድጋፍ በተቋሙ ለሚኖሩ ህጻናት እጅግ  አስፈላጊ በሆነበት ወቅት በመሆኑ ለሚኒስትር መስሪያ ቤቱ ምስጋናቸዉን አቅርበዋል፡፡የተደረገው ድጋፍ በሁሉም ክልሎች እና የከተማ አስተዳደሮች  የሴቶች፣ ህጻናትና ወጣቶች ቢሮዎች ስር ለሚገኙ  በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙ  ህጻናትን የሚንከባከቡ  ተቋማት ፣ ጥቃት ለደረሰባቸዉ ሴቶች  ለሚደግፉ ማዕከላት፣ የአዳሪ ትምህርት ቤት ሴት ተማሪዎች ፣ ከጎዳና ተነስተዉ በጊዜያዊ ማቆያ ለሚገኙ ህጻናት፣ ታዳጊዎችና ወጣቶች እንደሚዉል ለማወቅ ተችሏል፡፡

Write a Reply or Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *