loading
ም/ ጠ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን ስለ አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አፈጻፀም ከሕግ አስከባሪ አካላት ጋር ተወያዩ

ም/ ጠ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን ስለ አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አፈጻፀም ከሕግ አስከባሪ አካላት ጋር ተወያዩ

አዲስ አበባ፣ ሚያዚያ 5፣ 2012 ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ አቶ ደመቀ መኮንን አዋጁን ከሚያስፈፅሙ የመከላከያ ሰራዊት፣ ፌዴራል ፖሊስ፣ ብሔራዊ ደህንነትና ሌሎች የሕግ አስከባሪ ተቋማት አመራሮች ጋር  ውይይት አድርጓል፡፡አቶ ደመቀ  በውይይቱ መክፈቻ ላይ እንደተናገሩት በሽታውን ለመከላከል የዓለም ጤና ድርጅት መመሪያዎችን ተግባራዊ ማድረግ ያስፈልጋል ብለዋል።የኮቪድ 19 ቫይረስ ስርጭትን በመከላከል ሂደት ኢትዮጵያ ያወጣችው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተፈፃሚ እንዲሆንም የህግ አስከባሪ አካላት ትልቅ ሃላፊነት እንዳለባቸው አብራርተዋል።ውይይቱም በደንቡ መሰረት የተቋቋመው ኮሚቴ ሃላፊነትና የሕግ አስከባሪ ተቋማት በቅንጅት አዎንታዊ ስራዎችን በማከናወን ችግሩን ለመሻገር በሚያስችሉ ስራዎች ላይ የጋራ ግንዛቤ ለመፍጠር መሆኑን ገልጸዋል።

በውይይቱም የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ማስፈጸሚያ ደንብ ይዘት በተመለከተ በጠቅላይ አቃቤ ሕጓ ወይዘሮ አዳነች አቤቤ ቀርቦ ውይይት ተደርጎበታል።የኮቪድ 19 ወረርሽኝ ስርጭትን ለመከላከል፣ ለመቆጣጠርና የሚያስከትለውን ጉዳት ለመቀነስ ለወጣው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ማስፈፀሚያ ደንብ ይፋ ሆኗል።ማስፈፀሚያ ደንቡም አጠቃላይ አራት ዋና ዋና ክፍሎች ያሉት ሲሆን ይሄም ክልከላን የሚያስቀምጥ፣ ግደታዎችን የሚጥል፣ የአስፈፃሚ አካላትን ክንውን እንዲሁም ልዩ ልዩ ድንጋጌዎችን የያዘ መሆኑን ኢዜኣ ዘግቧል፡፡

Write a Reply or Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *