loading
የሽብር ቡድኑ በጭና እና ቆቦ ንፁሃንን በጅምላ ጨፍጭፏል – ሂዩማን ራይትስ ዎች ::

አዲስ አበባ፣ ታህሳስ 1፣ 2014 ሂዩማን ራይት ዎች የህወሓት የሽብር ቡድን በወረራ ይዟቸው በነበረው የአማራ ክልል ጭና እና ቆቦ ከተሞች ንፁሃን ዜጎችን በጅምላ መጨፍጨፉን ገለፀ፡፡ድርጅቱ ባወጣው ሪፖርት እንዳለው፥ የሽብር ቡድኑ ታጣቂዎች ከፈረንጆቹ ነሐሴ 31 እስከ መስከረም 9 ቀን 2021 ባለው ጊዜ ውስጥ በአማራ ክልል በያዛቸው አካባቢዎች በርካታ ንፁሃን ዜጎችን በጅምላ ገድሏል፡፡


ከዚህም ውስጥ የጭና ቀበሌ አንዱ ሲሆን፥ የአካባቢው ነዋሪዎች ለድርጅቱ እንደነገሩት የሽብር ቡድኑ ታጣቂዎች 26 ሰላማዊ ዜጎችን በግፍ ገድሏል፡፡ በቆቦ ከተማም እንዲሁ መስከረም 9 የህወሓት ታጣቂዎች በአራት የተለያዩ አጋጣሚዎች 23 ሰዎችን መግደላቸውን የዓይን እማኞች ተናግረዋል ነው ያለው ሪፖርቱ። የድርጅቱ የግጭት ዳይሬክተር ላማ ፋኪህ “የህወሓት ታጣቂዎች ለሰው ልጅ ህይወት እና ለጦርነት ህግጋት ያላቸውን ግድየለሽነትና ጭካኔ በእጃቸው ስር ያሉትን ሰዎች በመግደል አሳይተዋል ነው ያሉት።


እነዚህ ግድያዎችም በአማራ ክልሎች ተፈጽመዋል የተባሉ የጦር ወንጀሎችን በገለልተኛ አካል ማጣራት እንደሚያስፈልግ ያመላክታሉ ነው ያሉት ዳይሬክተሩ።
በሌላ በኩል ጦርነቱ በአማራ ክልል ከፍተኛ መፈናቀል አስከትሏል ያለው ሪፖርቱ፥ በክልሉ 3 ነጥብ 7 ሚሊዮን ሰዎች ሰብዓዊ እርዳታ ያስፈልጋቸዋል ሲልም አመላክቷል፡፡ ድርጅቱ የሽብርተኛው የህወሃት ታጣቂዎች አለም አቀፍ የሰብአዊነት ህግን በማክበር በሰላማዊ ዜጎች ላይ የሚደርሰውን ጥቃት በአስቸኳይ ማቆም አለባቸው ሲል አሳስቧል፡፡

Write a Reply or Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *