loading
በኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ቅዱስ ጊዮርጊስ በሰፊ የግብ ልዩነት አሸናፈ

በኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ቅዱስ ጊዮርጊስ በሰፊ የግብ ልዩነት አሸናፈ
የ10ኛ ሳምንት የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ጨዋታዎች ዛሬ በአዲስ አበባ እና ክልል ስታዲየሞች ተከናውነዋል፡፡
ቅዱስ ጊዮርጊስ ከ መከላከያ ባገናኘው ግጥሚያ ጊዮርጊስ 5 ለ 1 በማሸነፍ የነጥብ መጠኑን ወደ 15 ከፍ በማድረግ ደረጃውን ከአራተኛወደ ሶስተኛ አሻሽሏል፡፡
ለፈረሰኞቹ ድል ማድረግ በመጀመሪያው አጋማሽ ሳላዲን ሰዒድ እና ጌታነህ ከበደ እንዲሁም በሁለተኛው አጋማሽ ሙሉዓለም መስፍን፣ ጌታነህ ከበደ እና ሳሙኤል ተስፋዬ አገናኝተዋል፡፡ ለጦሩ ቡድን በኃይሉ አሰፋ በራሱ ግብ ላይ አስቆጥሯል፡፡
ሁለቱ ቡድኖች በኢትዮጵያ ዋንጫ አንደኛ ዙር ተገናኝተው መከላከያ 1 ለ 0 መርታቱ ይታወሳል፡፡
ክልል ላይ በተደረጉ ግጥሚያዎች በአዳማ አበበ ቢቂላ ስታዲየም አዳማ ከተማ በዳዋ ሆቴሳ ብቸኛ ግብ ድሬዳዋ ከነማን 1 ለ 0 ረትቷል፤ ሀዋሳ ደግሞ በሜዳውና ደጋፊው ፊት በመቐለ 70 እንደርታ የአማኑኤል ገብረሚካኤል ግብ በተመሳሳይ 1 ለ 0 ተሸንፏል፡፡
በባህር ዳር ግዙፍ ስታዲየም ደግሞ ባህር ዳር ከነማ እንግዳውን ደደቢትን 2 ለ 0 አሸንፏል፡፡ ለጣናው ሞገድ ኤፍሬም ጌታቸው በራሱ ግብ ላይ እና ጃኮ አራፋት ከመረብ አገናኝተዋል፡፡
ነገ ደግሞ ሶስት ጨዋታዎች ክልል ላይ በሚገኙ ስታዲየሞች ሲከናወኑ፤ የሊጉ መሪ ኢትዮጵያ ቡና ወደ ሀዋሳ አቅንቶ በሀዋሳ ሰው ሰራሽ ስታዲየም ከ ሲዳማ ቡና ጋር ይፋለማል፡፡ ኢንተርናሽናል አርቢትር አማኑኤል ኃይለ ሥላሴ ደግሞ ጨዋታውን በዳኝነት ይመሩታል፡፡
ሶዶ ላይ ወላይታ ድቻ ከ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ሲጫወቱ ሽረ ላይ ስሑል ሽረ ከ ደቡብ ፖሊስ ይገናኛሉ፡፡ ሁሉም ግጥሚያዎች በተመሳሳይ 9፡00 ይደረጋሉ፡፡
በ10ኛ ሳምንት የሊጉ መርሃግብር ዛሬ ጅማ አባ ጅፋር ከ ፋሲል ከነማ ሊደረግ የነበረው ጨዋታ ጅማ አባ ጅፋር በኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ከሞሮኮው ሀሳኒያ አጋርዲን ጋር የሚጫወት በመሆኑ ወደ የካቲት 17 ተገፍቷል::
በሊጉ የደረጃ ሰንጠራዥ ኢትዮጵያ ቡና በ18 ነጥቦች ቀዳሚ ነው፤ ሀዋሳ ከነማ በ17 ይከተላል፤ ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ባህር ዳር ከነማ በዕኩል 15 ነጥቦች በግብ ክፍያ ተበላልጠው ሶስተኛና አራተኛ ደረጃን ተቆናጥጠዋል፡፡
የሰዲማ ቡናው አጥቂ አዲስ ግደይ እና የአዳማው ዳዋ ሆቴሳ በተመሳሳይ ሰባት ጎሎች ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን ይመራሉ፡፡

Write a Reply or Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *