loading
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከሜቴክ ጋር የስራ ግንኙነት እንዳልነበረው አስታወቀ

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከሜቴክ ጋር የስራ ግንኙነት እንዳልነበረው አስታወቀ

አርትስ 14/03/2011

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከዚህ በፊት አስለምዶት ከማያውቀው ውጭ ለመገናኛ ብዙሀን በአጠቃላይ ከአየር መንገዱ ጋር በተገናኙ ጉዳዮቸ  መግለጫ ሰጥቷል፡፡

መግለጫውን የሰጡት የአየር መንገዱ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ተወልደ ገ/ማርያም እና የስራ ኃላፊዎች ለተነሱ ጥያቄዎች ምላሽ ሰጥተዋል፡፡

አቶ ተወልደ ገ/ማርያም የሰራተኞችን አያያዝ በተመለከተ ለሚነሱ ቅሬታዎች  በሰጡት ምላሽ አየር መንገዱ ከ16 ሺ በላይ ቋሚና ኮንትራት ሰራተኞች አሉት፤ ድርጅቱም ዲሲፕሊን ላይ ድርድር የማያውቅ በመሆኑ ሰራተኞች እነዚህን ሲተላለፉ ቅጣት ይጣልባቸዋል፤ በተጨማሪም ከክህሎትና ዕውቀት ማነስ ጋር ተያይዞ በሚሰጡ ምዘናዎች አነስተኛ ሲሆኑ ቅሬታ ይፈጠራል ከዚያ ማህበራዊ ሚዲያዎችን በመጠቀም የውሽት ዜናዎችን ያሰራጫሉ በማለት ተናግረዋል፡፡

እኛም ስራ ስለሚበዛብን ለሁሉም ለሚነሱ ቅሬታዎችና አሉባልታዎች ምላሽ ከመስጠት ተቆጥበናል በማለት ገልፀዋል፡፡

አቶ ተወልደ የሰራተኞች ቅሬታዎች የሚስተናገዱበት አሰራር አለን ያሉ ሲሆን፤ ዘርን ተገን አድርገን ሰራተኛን አላሰናበትንም፤ አየር መንገዱም የሁሉም ኢትዮጵያውያን ነው ብለዋል፡፡

ከሜቴክ የአውሮፕላን ግዥና ተያያዥ ጉዳዮች ጋር ተጠይቀው፤ ምንም የምናውቀው ጉዳይ የለም፤ ከሜቴክ ጋርም ቢሆን የስራ ግንኙነት ኖሮን አያውቅም ሲሉ አረጋግጠዋል፡፡

በቱሪዝም ላይ አየር መንገዱ የሚያበረክተውን አስተዋፅኦ ለማሳደግ በ65 ሚሊየን ዶላር ወጪ ደረጃውን የጠበቀ ሆቴል በቅርቡ ያጠናቅቃል፤ ሌላም ተጨማሪ ሆቴል እንደሚገነባ ዋና ስራ አስፈፃሚው አስታውቀዋል፡፡

አየር መንገዱ በተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት የአየር መንገድ ድርሻ በመግዛት፣ በማስተዳደር፣ በማማከር እና በማቋቋም እየሰራ እንደሆነና በሀገር ኢኮኖሚ ላይም ትልቅ አስተዋፅኦ አለው ተብሏል፡፡ እንደ ስራ አስፈፃሚው ገለፃ  አየር መንገዱ ከመገናኛ ብዙሀን ጋር ያለውን ቅርበት የተሻለ ለማድረግም ይሰራል፡፡

Write a Reply or Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *