loading
ሮናልዶ የግሎብ ሶከር ሽልማትን ለሶስት ተከታታይ ዓመት አሸነፈ

ሮናልዶ የግሎብ ሶከር ሽልማትን ለሶስት ተከታታይ ዓመት አሸነፈ
ግሎብ ሶከር አዋርድ በዓመቱ በእግር ኳስ ዘርፍ በተለያዩ የሽልማት ዘርፎች ጥሩ ጊዜ የነበራቸውን ግለሰቦች ከ2010 አንስቶ መሸለም የጀመረ ሲሆን የሽልማት አሰጣጡ ለወኪሎችና ስፖርቲንግ ዳይሬክተሮች እና ለልዩ ተሸላሚ ክብር በመስጠት ተጀምሯል፤ በየዓመቱም የተለያዩ ዘርፎችን በመመስረት ለዘጠኝ ዓመታት ዘልቋል፡፡
የሽልማቱ ባለቤቶች የአውሮፓ የወኪሎች ህብረት እና የአውሮፓ የክለባት ህብረት ናቸው፡፡
የ2018 የግሎብ ሶከር ሽልማት ትናንት በዱባይ ሲከናወን የዩቬንቱሱ ሮናልዶ የአትሌቲኮው ማድሪዱን አንቷን ግሪዝማንና የፒ.ኤስ.ጂውን ክልያን ምባፔ በመብለጥ የዓመቱ ኮከብ ተጫዋች ተብሏል፡፡ የትናንቱ ሽልማት በአጠቃላይ ለአምስተኛ ጊዜ የተቀዳጀው ክብር ሲሆን በተከታታይ ደግሞ ሶስተኛው ሁኗል፡፡ ቀሪዎቹን በ2012 ራድማይል ፋልካኦ፣ ፍራንክ ሪቤሪ በ2013 እንዲሁም ሊዮኔል ሜሲ በ2015 አሸናፊ ሁነዋል፡፡
በትናንትናው የዱባይ ኢንተርናሽናል ስፖርትስ ኮንፈረንስ የሽልማት ስነ ስርዓት ሮናልዶ የደጋፊዎችን ሽልማት ያሸነፈ ሲሆን ሮናልዶንና ሌሎች ኮከቦችን ጨምሮ በወኪልነት እያገለገለ የሚገኘው ሆርሄ ሜንዴዝ ኮከብ ወኪል አሊያም ኮከብ ደላላ ተብሏል፡፡
የፈረንሳይ ብሔራዊ ቡድንን ለዓለም ዋንጫው ክብር ያበቁት አሰልጣኝ ዲዲዬ ዴሾ የዓመቱ ኮከብ አሰልጣኝ ይገባዎታል ተብለዋል፤ ብራዚላዊው ሮናልዶ ሊዊዝ ናዛሪዮ ዴ ሊማና ፈረንሳዊው ብላሴ ማቹዲ የተጫዋችነት ዘመን ሽልማት ሲበረከትላቸው፤ የቀድሞው የክሮሽያ ተጫዋችና የፊፋ ምክትል ፀሃፊ ዝኖሚር ቦባን ልዩ ተሸላሚ ተብሏል፡፡ የዩቬንቱሱ ፋቢዮ ፓራቲክ ኮከብ ስፖርቲንግ ዳይሬክተር ተሰኝተዋል፡፡
የስፔኑ አትሌቲኮ ማድሪድ የዓመቱ ምርጥ ቡድን ተብሏል፡፡

Write a Reply or Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *